24/04/2026
አርብ:- ሚያዚያ 16 ቀን 2018 ዓ.ም
የክህሎትና የትብብር ድልድይ፦ 16ኛው የቴክኒክና ሙያ ሳምንት በታላቅ የፓናል ውይይት ደመቀ!!
የሀገርን ምጣኔ ሀብት በዕውቀትና በክህሎት ለመገንባት በሚደረገው ጉዞ ውስጥ የቴክኒክና ሙያ ዘርፍን ከኢንዱስትሪው ጋር ማስተሳሰር የውዴታ ሳይሆን የህልውና ጉዳይ ሆኗል። ይህንን ታላቅ ዓላማ ስንቅ ያደረገው 16ኛው የቴክኒክና ሙያ ሳምንት ‹‹የቴክኖሎጂ እድገት ለአገር ብልጽግና›› በሚል መንፈስ ደማቅ የፓናል ውይይትን አስተናግዷል።
በመድረኩ ላይ የአዲስ አበባ ስራና ክህሎት ቢሮ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎችን ጨምሮ፣ የዘርፉን ትንፋሽ የሚወስኑ የኢንዱስትሪ መሪዎች፣ የመንግስት የልማት ድርጅቶች፣ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ምሁራን፣ የሲቪክ ማህበራት እና ሞዴል ኢንተርፕራይዞች ተገኝተዋል። ይህ ውይይት በራሱ በዘርፉ ላይ ያለውን ከፍተኛ ተስፋና ትኩረት የሚያሳይ ነበር።
የፓናል ውይይቱ በሁለት መሳጭና ወቅታዊ መነሻ ፅሁፎች ላይ ያተኮረ ነበር፡፡ በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል የኢትዮጵያ ፓወር አካዳሚ መሪ ዶ/ር ወንድወሰን ካሳ "ከፕሮጀክት ወደ አጋርነት መሸጋገር" በሚል ርዕስ ባቀረቡት ጥንካሬ ያለው ሃሳብ፤ ትብብሮች በጊዜያዊ ፕሮጀክቶች ብቻ ሳይታጠሩ እንዴት ወደ ዘላቂና ስልታዊ አጋርነት ማደግ እንዳለባቸው በስፋት ዳስሰዋል። በዚህም ትብብር ለጋራ ስኬት የሚገነባ ድልድይ እንጂ ለጊዜው የሚቆም ጥላ አለመሆኑን አሳተዋል፡፡
በሌላ በኩል የፌደራል ቴክኒክና ሙያ አሰልጣኝ ዶ/ር ገነነ አበበ በበኩላቸው "የአጠቃላይ ትምህርትን በሙያ ስልጠና ማዳበር" በሚለው ሃሳባቸው መደበኛው ትምህርት ከተግባር ተኮር ክህሎት ጋር ሲዋሃድ የሚፈጥረውን ብቁ ዜጋ ለተሳታፊው አሳይተዋል።
መድረኩ በሁለቱ ምሁራን ሃሳብ ላይ ተመስርቶ በጋለ ጥያቄና መልስ እንዲሁም ገንቢ በሆኑ አስተያየቶች የበለጸገ ውይይት ተካሂዶበታል።
ከቃላት ባለፈ ተግባርን ምስክር ያደረገው የቴክኖሎጂ ኤግዚቪሽን የዕለቱ ሌላኛው ድምቀት ነበር። በኮሌጁ አሰልጣኞችና ሰልጣኞች በላብና በጥበብ የተሰሩ የቴክኖሎጂ ውጤቶች ለእይታ የቀረቡ ሲሆን አጋር አካላትም አገልግሎቶቻቸውንና ምርቶቻቸውን አስተዋውቀዋል። ይህም የቴክኒክና ሙያ ተቋማት ለኢንዱስትሪው የሚበጁ የፈጠራ ውጤቶች ምንጭ መሆናቸውን በተጨባጭ ያረጋገጠ መድረክ ሆኖ አልፏል።
‹በላቀ አገልግሎት የመረጃ ተደራሽነት››