20/08/2026
የሀኪም ግዛው ሆስፒታል በአጣዬ ከተማ ነፃ የቀዶ ሕክምና ዘመቻ ማካሄድ ጀመረ
============================
የደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ አስራት ወልደየስ ጤና ሳይንስ ካምፓስ ሀኪም ግዛው ሆስፒታል፣ ከአጣዬ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል ጋር በመተባበር በክረምት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት መርሃ ግብር በአጣዬ ከተማ ነፃ ምርመራና የቀዶ ሕክምና ዘመቻ ማካሄድ ጀምሯል።
በዘመቻው ላይ የአስራት ወልደየስ ጤና ሳይንስ ካምፓስ የሕክምና ትምህርት ቤት ዲን ዶ/ር አሰፋ ፋንታሁንን ጨምሮ የተለያዩ የሕክምና ባለሙያዎችን ያካተተ የቀዶ ሕክምና ቡድን በስፍራው ተገኝቷል።
ቡድኑ በዘመቻው ወቅት የእንቅርትና የአንገት አካባቢ እጢዎች፣ የሐሞት ጠጠር፣ የአንጀትና የፊንጢጣ አካባቢ ችግሮች እንደ ፊስቱላና ኪንታሮት፣ በተለያዩ የሰውነት አካባቢዎች የሚከሰቱ እብጠቶች፣ የጡት ካንሰር፣ የትርፍ አንጀት ችግሮች፣ የድንገተኛ ሕክምና፣ በእግር ላይ የሚታዩ የደም ሥር ችግሮች እንዲሁም የሽንት ቱቦ እጢዎችና የተለያዩ ችግሮች ላይ ነፃ ምርመራና የቀዶ ሕክምና አገልግሎት ይሰጣል።
የሕክምና ቡድኑ ከነሐሴ 13 እስከ 19 ቀን 2018 ዓ.ም ድረስ ለሰባት ተከታታይ ቀናት በአጣዬ ከተማ በመቆየት፣ ከአጣዬ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል የጤና ባለሙያዎች ጋር በመሆን ለከተማው ማኅበረሰብ አገልግሎቶችን በነፃ እንደሚሰጡ ታውቋል።
በተያያዘ ዜና በዚሁ የክረምት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት መርሃ ግብር የሀኪም ግዛው ሆስፒታል የጤና ባለሙያዎች ቡድን ወደ ሀገረ ማሪያም ከሰም ወረዳ ቱለፋ ከተማ አስተዳደር በመሄድ ለከተማው ማህበረሰብ የተለያዩ የጤና ምርመራና የሕክምና አገልግሎቶችን በነፃ እየሰጠ ይገኛል። በተጨማሪም ቡድኑ ለማህበረሰቡ የጤና ግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎችን ያከናውናል፡፡
*************************
ነሐሴ 14 ቀን 2018 ዓ.ም
የሕዝብ ግንኙነትና ኮሙኒኬሽን ቡድን
ታዓማኝ እና ወቅታዊ መረጃዎችን ለማግኘት:-
በፊስቡክ ፡- https://www.facebook.com/profile.php?id=100087595710493
በቴሌግራም፡- https://t.me/asratcampus
በዩቲዩብ ገጻችን፡- www.youtube.com/
ቲክቶክ፡- https://www.tiktok.com/
ዌብሳይት፡ https://www.dbu.edu.et/campus/awhsc/awhsc_latest በመወዳጀት ይከታተሉን፡