08/07/2025
አንድ የመንደር ወጣት ከሱ ሰፈር የሆነችውን ቁጥብ፣ በጎ እና ሃይማኖተኛ የሆነች ልጅ አገባ። ከተጋቡ ገና አንድ ዓመት እንደሞላቸው ወጣቱ ከአንድ የቅርብ ዘመዱ ጋር ከባድ ግጭት ውስጥ ገባና በከፍተኛ ንዴት ምክንያት ገደለው።
ሰውየውም ከሚስቱ ጋር አካባቢያቸውን ለቆ በመውጣት ራቅ ባለ የገጠር ቀበሌ ውስጥ ከአዲስ ማህበረሰብ ጋር አዲስ ህይወት መኖር ጀመረ።
ወጣቱ የጎጡን ሹም (መሪ) የመሰብሰቢያ ቦታ ያዘወትር ነበር፤ እንደተለመደውም በውይይቶች ይሳተፋል፣ ምክር ይጠይቃል፣ ያወጋ። አንድ ቀን ሹሙ በወጣቱ ቤት አጠገብ ሲያልፍ ቁጥብ፣ ውብና ክብር ያላትን ሚስቱን ለመጀመሪያ ጊዜ አያት።
በዚያች ቅጽበት በሹሙ ልብ ውስጥ ምኞት ተቀጣጠለ። ክፉ አባዜ ተጠናወተውም ባሏን ወደ ጉዞ ልኮ ሚስቱን ብቻዋን በማግኘት ርኩስ ፍላጎቱን ለመፈጸም ክፉ እቅድ አወጣ።
ከጥቂት ቀናት በኋላ በመሰብሰቢያው ቦታ ሹሙ ጉዳዩን አንስቶ እንዲህ አለ፦ "በአንድ አካባቢ በጣም ጥሩ የግጦሽ መሬት እንዳለ ሰምቻለሁ። ጥቂት ሰዎች ሄደው እንዲያዩልኝ እፈልጋለሁ።" ወጣቱንም ጨምሮ አራት ሰዎችን መረጠ። ጉዞው ጥቂት ቀናትን የሚወስድ ነበርና አራቱም ጉዟቸውን ጀመሩ።
በዚያች ሌሊት ሹሙ በድብቅ ወደ ወጣቱ ቤት ሄደ። በጨለማ ውስጥ ግድግዳ ለግድግዳ ሲሄድ ድምጽ ስላሰማ ሚስትየዋ ነቃች። ደንግጣ፣ "ማን ነው?" ስትል ጠየቀች። ሹሙም ማንነቱን ገለጸ።
እሷም፣ "በዚህ ሰዓት? ሁሉ ሰላም ነው?" ስትል ጠየቀች።
ሹሙም የልቡን እንዲህ ሲል ተናገረ፦ "ካየሁሽ ቀን ጀምሮ ልቤ ሰላም አጥቷል። እፈልግሻለሁ፤ የኔ ሁኚ።"
ሴትየዋ በታላቅ ክብር እንዲህ መለሰች፦ "እሺ፣ ይህን በእውነት ከፈለግክ፣ በመጀመሪያ አንድ ጥያቄ መልስልኝ። በትክክል ከመለስክ፣ እንደ ምኞትህ ይሆናል።"
ሹሙ ተደስቶ፣ "ጠይቂ!" አላት።
እሷም አለች፦ "ስጋ እንዳይበላሽ ለመጠበቅ ጨው እንደሚያገለግለው ሁሉ፣ ንገረኝ፣ ጨው ራሱ ቢበላሽ… በምን ይጣፍጣል?" (ወይም ማን ያነጻዋል?)
ሹሙ በጥልቅ ሃሳብ ውስጥ ገባ።
አንድ ሙሉ ቀንና ሌሊት ቢያስብም መልሱን ሊያገኝ አልቻለም።
በማግስቱ በመሰብሰቢያው ቦታ ያንኑ ጥያቄ ለሁሉም አቀረበ፣ ነገር ግን አጥጋቢ መልስ አላገኘም።
አንድ በዕድሜ የገፉ ሽማግሌ ጥግ ላይ በሃሳብ ተውጠው ተቀምጠው ነበር።
ሹሙም፣ "እርስዎ ለምን አይመልሱም?" ሲል ጠየቃቸው።
ሽማግሌውም እንዲህ አሉ፦ "ምክንያቱም ይህ ጥያቄ ብቻ ሳይሆን የጥንት ጥበብ መልዕክት ነውና… ልታዋርድህ፣ ልታሳፍርህ ትችል ነበር፣ ነገር ግን በምትኩ በጥያቄ ህሊናህን ቀሰቀሰች።"
ከዚያም ሽማግሌው ቀጠሉ፦ "ስጋ ሲበላሽ ጨው ይጠብቀዋል። ነገር ግን ጨው ራሱ ከተበላሸ ማን ያድነዋል? ማለትም… ተራው ህዝብ ሲሳሳት እንደ አንተ ያሉ ሹሞች ወደ ጥሩ መንገድ ይመሩታል፤ ነገር ግን ሹሙ ራሱ ከተሳሳተ/ከጠመመ ማን ያስተካክለዋል?"
ይህን ሲሰማ የሹሙ አንገት በሀፍረት ተደፋ፣ አይኖቹም በእንባ ተሞሉ።
እንዲህም አለ፦ "እግዚአብሔር ይጠብቅልኝ። አይኔን ገልጠውልኛል። እግዚአብሔር እንደሚሰውር፣ ስህተቴን ሰውሩልኝ።"
ስጋ በጨው ይድናል፣
ጨው ራሱ ቢበላሽ…
በምን ይድናል?
እኔም እላለሁ፦
አባት ሲሳሳት—ልጆችን ማን ይመራል?
መምህር ሲሳሳት—እውቀትን ማን ያስተምራል?
መሪ ሲሳሳት—ሀገርን ማን ያድናል?
ሁሌም አስታውስ፣ ከጠቢባን ጋር መቀመጥን ተማር።
የሞኞች ስብስብ ልብን ማበላሸት ብቻ ሳይሆን ትውልድንም ያጠፋል።