22/07/2026
"በክልሉ የዶሮ አቅርቦትና ግብይት ማነቆዎችን ለመፍታት እየተሠራ ነው!" ዶ/ር አባይነህ ኬዳ
በክልሉ ግብርና ቢሮ የእንስሳትና ዓሣ ሀብት ልማት ዘርፍ ከደቡብ ኢትዮጵያ ዶሮ እርባታ ኢንተርፕራይዝ ጋር በመቀናጀት በክልሉ ዞኖች የፍላጎት ዳሰሳና የግንዛቤ መፍጠር ሥራዎችን በመገምገም ግብረ-መልስ ሰጥቷል።
በክልሉ ግብርና ቢሮ የእንስሳትና ዓሣ ሀብት ልማት ዘርፍ በክልሉ የሌማት ትሩፋት ኢኒሼቲቭ ግቦችን ለማሳካት ከሚከናወኑ ተግባራት መካከል የዶሮ ሀብት ልማትን ማፋጠን አንዱ መሆኑ ይታወቃል።
በክልሉ ቀደም ሲል ሲስተዋል የነበረ የዶሮ አቅርቦት ተግዳሮትን በመሠረታዊነት ለመቅረፍ ይቻል ዘንድ ክልሉ የራሱን የዶሮ እርባታ ኢንተርፕራይዝ አቋቁሞ ወደ ትግበራ መገባቱ ይታወሳል።
ይህንኑ ተከትሎ በወላይታ ሶዶ የወላጅ ዶሮ እርባታና ማሰራጫ ማዕከል ተቋቁሞ የአንድ ቀን ዕድሜ የዶሮ ጫጩት፣ ቄብና ኮከኔ የማምረትና የማሰራጨት ሥራ እየተሠራ ይገኛል።
ኢንተርፕራይዙ በመስኩ ሲስተዋል የቆየውን የአቅርቦትና ግብይት ተግዳሮቶችን ለመቅረፍ የሚችል አቅም ቢገነባም አቅርቦቱ ከፍላጎቱ ከፍያለ ሆኖ በመገኘቱ ያለውን ክፍተቱን ለመሙላት ከእርባታ ኤክስቴንሽኑ ጋር በቅንጅት እንዲሠራ አቅጣጫ ተቀምጧል።
በዚሁ መሠረት በክልሉ ግብርና ቢሮ የእንስሳትና ዓሣ ሀብት ልማት ዘርፍ የድጋፍና ክትትል ቡድን ከኢንተርፕራይዙ ጋር በመቀናጀት በክልሉ ዞኖች የሚስተዋለውን የዶሮ ፍላጎት ከመለየት በተጨማሪ ግንዛቤ የመፍጠር ተግባራትን በማከናወን በተገኙ ጭብጦች ዙሪያ የጋራ መድረክ በመፍጠር ግብረ-መልሶችን ሰጥቷል።
የክልሉ ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊና የእንስሳትና ዓሣ ሀብት ልማት ዘርፍ ኃላፊ ዶ/ር አባይነህ ኬዳ በክልሉ ዶሮ አርቢ ኅብረተሰብ ዘንድ ሰፊ ፍላጎት ቢኖርም አቅርቦቱን ከግብይት ጋር ከማስተሳሰር አንፃር ተግዳሮቶች መስተዋላቸውን ገልፀዋል።
ዶ/ር አባይነህ ተግዳሮቱን ለመቅረፍ የእርባታ ኢንተርፕራይዙ ከኤክስቴንሽኑ ጋር ተሸናጅቶ ኤንዲሠራ በተቀመጠው አቅጣጫ መሠረት ዘርፉ ሥራዎችን እየከወነ እንደሚገኝ ገልፀው ለድጋፍና ክትትል ቡድኑ በተሰጠው ተልዕኮ መሠረት ተግባራት በቅንጅት ተፈፅመው ግብረ-መልስ በሠሰጠቱ ምስጋና አቅርበዋል።
የደቡብ ኢትዮጵያ ዶሮ እርባታ ኢንተርፕራይዝ ዋና ሥራ አስኪያጅ ዶ/ር አዲሱ ኢዮብ በበኩላቸው ኢንተረፕራይዙ Tetra-H የተሰኘ የተሻሻለና ምርታማ የሆነ የወላጅ ዶሮ ዝርያ እርባታና ማሰራጫ ማዕከል በወላይታ ሶዶ ማዕከል በመክፈት የአንድ ቀን ዕድሜ የዶሮ ጫጩቶችን ጨምሮ ቄብና ኮከኔዎችን እያመረተ እንደሚገኝ ገልፀው ምርቱን ከማሰራጨት አንፃር ተግዳሮት ሲገጥም እንደቆዬ ተናግረዋል።
የገጠመውን ተግዳሮት ለመቅረፍ ይቻል ዘንድ ኢንተርፕራይዙ ከክልሉ እንስሳትና ዓሣ ሀብት ልማት ዘርፍ ጋር በመቀናጀት ፍላጎትና ግንዛቤ የመፍጠር ሥራ እስከ ዞን ወርዶ ማከናወኑን አብራርተዋል።
የወላጅ ዶሮ እርባታ ማዕከሉ በአሁኑ ወቅት ለክልሉ ዶሮ አርቢ ኅብረተሰብ የሚበቃ አቅርቦት በእጁ እንደሚገኝ የጠቆሙት ዶ/ር አዲሱ ለማዕከሉ የሚቀርብ ማናቸውም ጥያቄ እንደሚስተናገድ አመልክተው የድጋፍና ክትትል ቡድኑን አመስግነዋል።
አክለውም የተሰጠው ግብረ-መልስ ቅቡልነት ያለውና በቀጣይ የሚያሠራ መሆኑን አመልክተው የተጀመረው ቅንጅታዊ አሠራር ተጠናክሮ እንዲቀጥል ጠይቀዋል።
በመድረኩ ዶ/ር አባይነህ ኬዳን እና ዶ/ር አዲሱ ኢዮብን ጨምሮ የክልሉ እንስሳትና ዓሣ ሀብት ልማት ዘርፍ እና የዶሮ እርባታ ኢንተርፕራይዙ ከፍተኛ ባለሙያዎች መሳተፋቸው ተዘግቧል።
በአያሌው ዘነበ