31/10/2024
ሐዋርያ ጳውሎስ ዛሬ ቢኖር ምን ይለን ይሆን?
2. የቤተ ክርስቲያን አንድነት እንዳያፈርሱ የተሰጠ ጠንካራ ማስጠንቀቂያ(1 ቆሮ 3፡16-17)
ጳውሎስ እንደገና ሌላ ምሳሌያዊ ዘይቤ ስለ ቤተ ክርስቲያን ሲጠቀም እንመለከታለን፡፡ በመጀመሪያ በ3፡5-9 ጳውሎስ ቤተ ክርስቲያንን ከእርሻ ጋር ሲያመሳስል፣ ከዚያም 3፡10–15 ቤተ ክርስቲያንን በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ የተመሠረተች ሕንጻ አስመስሎ በሦስተኛ ደረጃ የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያ ከሆነ ከእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ጋር አመሳስሏቸዋል። እዚህ ላይ “እናንተ” የሚለው ቃል ብዙ ቁጥር እንጂ ነጠላ አለመሆኑን መረዳት ያስፈልጋል።
ቤተ ክርስቲያን ወይም የክርስቲያኖች ህብረት የእግዚአብሔር መንፈስ ማደሪያ ቤተ መቅደስ ነው፡፡ የእግዚአብሔር መንፈስ በእያንዳንዱ አማኝ ውስጥ በግለሰብ ደረጃ በውስጡ ይኖራል(1ኛ ቆሮንቶስ 6፡19)፤ ነገር ግን ጳውሎስ በዚህ ጥቅስ ውስጥ እየተናገረ ያለው ስለ እያንዳንዱ አማኝ የግል ሕይወት ሳይሆን ቤተ ክርስቲያን በመባል የሚታወቁትን የተሰበሰቡ የአማኞች ህብረትን ነው፡፡ ስለዚህም በህብረት ለመገናኘት ሥጋዊ መዋቅር ባይኖራቸውም በክርስቶስ የመስቀል ላይ ሥራ የተሰበሰቡ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ይሆናሉ። ቤተ ክርስቲያን በክርስቶስ መስቀል የተወለደች ስሆን የኢየሱስ ተከታዮች ከእሱ ጋር የተያያዙ የአካሉ ክፍሎች ናቸው። ክርስቲያኖች ብዙ ጊዜ እንደሚሉት “ቤተ ክርስቲያን” ሕንፃው ሳይሆን ሕዝብ ነው። ስለዚህ ይህ ህብረትን አቅልሎ በመመልከት በዓለም ጥበብ፣ የግል ፍላጎትና መከፋፈል እንዳትፈርስ ይህ ክፍል ጠንካራ ማስጠንቀቂያ ይሰጣል።
ቁጥር 16 የቆሮንቶስ ቤተ ክርስቲያን የእግዚአብሔር መንፈስ ያደረባት ቤተ መቅደስ ነበረች። ጳውሎስ እዚህ ላይ እየተናገረ ያለው ሁለንተናዊቷ ቤተ ክርስቲያን የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ እንደሆነች ነው (ኤፌ. 2፡19-22፤ 1 ጴጥ. 2፡ 5)፡፡ ህብረቱን የእግዚአብሔር መቅደስ የሚያደርገው የመንፈስ ማደሪያ መሆኑ ብቻ ነው፡፡ መንፈስ ቅዱስ የሌለባት ከሆነ እንደማንኛውም ህብረት ወይም እድር ነው፡፡
3፡17 ማንም የጌታ አገልጋይ ቤተ ክርስቲያንን ከማነጽ ይልቅ ቢያፈርስ እግዚአብሔር ያፈርሰዋል (ሐዋ. 9፡1-4)። የተቀደሰ ቤተመቅደስን ማፍረስ ወይም ማበላሸት በጣም ከባድ ነገር ነው። በጥንቱ ዓለም ቤተመቅደስን ማፍረስ ትልቅ ወንጀል ነበር። ቤተ ክርስትያን ቅድስተ ቅዱሳን ናትና ምንም እንኳን በአኗኗሯ ሁልጊዜ እንደ ጥሪዋ ቅዱስ ባትሆንም እግዚአብሔር ራሱን እንዲያከብር ለብቻ ለይቷታል፡፡ አንድ አገልጋይ ቤተ ክርስቲያንን ሊያፈርስ የሚችለው ህብረታቸውን በማናጋትና በክርስቲያኖች መካከል ክፍፍል እንዲፈጠር በማድረግ ነው፡፡ ያንን የሚያደርገውን ማንም ሰው እግዚአብሔር ሳይቀጣው አይተወውም፡፡
እግዚአብሔር ለቤተ ክርስቲያን የሚጠነቀቀው ቤተ መቅደሱ ስለሆነችና የመንፈሱ ቅዱስ ማደሪያ ስለሆነች የራሱን ቅድስና ይጠብቃል። ስለዚህ ማንም የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ ቢያፈርስ እግዚአብሔር ያንን ሰው ያፈርሰዋል። እርሱ በኢየሱስ መሠረት ላይ ደካማ የሚገነቡትን መሪዎችን ብቻ ሳይሆን ቤተ ክርስቲያንን ሙሉ በሙሉ ስለሚያፈርስ ምናልባትም በሐሰት ትምህርት ወይም ሕዝቡን አንድ ከማድረግ ይልቅ እየከፋፈሉ ስላሉ አገልጋዮች ተናግሯል። እግዚአብሔር ያንን ሰው ያጠፋዋል። ይህ ማለት የዚህን ሰው ሥጋዊ ሕይወት ያቆማል ወይስ ይህ ሰው ለዘላለም ይኮንናል ማለት ነው? ጳውሎስ አልገለጸም፣ ነገር ግን በግልጽ የተናገረለት የእግዚአብሔርን ጨካኝ እና አሳማሚ ፍርድ ለማመልከት ነው። አዲስ ኪዳንን ሰፋ አድርገን ስንመለከት እግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን አሳዳጆችን በሕይወት እንዲተርፉ ሊፈቅድ እንደሚችል ያሳያል፣ ነገር ግን ሁሉም ሰዎች በክርስቶስ እና በቤተክርስቲያኑ ላይ ስላላቸው ምግባራቸው የዘላለም ፍርድ ይጠብቃቸዋል (ራዕይ 20፡11-15)።
1 ቆሮንቶስ 3፡5-17 አንድ ላይ ስታይ ጳውሎስ ስለ ሦስት ዓይነት ግንበኞች ይናገራል፡ ጥበበኞች (ቁ. 12 እና 14)፣ ጥበብ የጎደላቸው ሰነፎች (ቁ. 15)፣ እና ሕንፃውን የሚጎዱ ደንቆሮዎች (ቁ. 17)። ሁሉም የእግዚአብሔር አገልጋዮች በቆሮንቶስ ይሠሩት የነበረውን ሥራ አስፈላጊነት ለማጉላት ጳውሎስ ስለ ቤተ ክርስቲያን (ቁ. 5-17) አንድነት በማጉላት እያንዳንዱ አገልጋይ አንድነቱን ለማነጽ በሚኖራ ሚና መሠረት ተገቢውን ሽልማት ወይም ቅጣት ይቀበላል፡፡ ቤተ ክርስቲያን የእግዚአብሔር ቅዱስ ቤተ መቅደስ በመሆኗ እግዚአብሔር ለራሱ ክብርና ለቤተ አንድነት ይጠነቀቃል፡፡
እኛስ የእግዚብሔር ቤተ መቅደስ ቅድስና አንድነቷን የጠበቀች እንድትሆን ምን አስተዋጽኦ እያበረከትን ነው?
ሐዋርያ ጳውሎስስ ዛሬ ቢኖር ምን ይለን ይሆን?
ሐዋርያ ጳውሎስ ዛሬ ቢኖር ምን ይለን ይሆን? 2. የቤተ ክርስቲያን አንድነት እንዳያፈርሱ የተሰጠ ጠንካራ ማስጠንቀቂያ(1 ቆሮ 3፡16-17) ጳውሎስ እንደገና ሌላ ምሳሌያዊ ዘይቤ ስለ ቤተ ክርስቲያ...