30/07/2022
ሪፍት ቫሊ ዩኒቨርሲቲ ባሕርዳር ካምፓስ በተለያዩ የሙያ ዘርፎች ያሰለጠናቸውን ተማሪዎች አስመረቀ ።
ባሕር ዳር: ሐምሌ 23/2014 ዓ.ም ዩኒቨርስቲው ለ8ኛ ጊዜ በመደበኛና በርቀት በፋርማሲ፣ በነርስ፣ በቢዝነስ ማኔጅመንትና በአካውንቲንግ በመጀመሪያ ዲግሪ ያሰለጠናቸውን 269 ሰልጣኞችን እያስመረቀ ነው።
በሪፍት ቫሊ ዩኒቨርሲቲ የባሕርዳር ካምፓስ ዲን እስማኤል የሱፍ እንዳሉት ተመራቂዎች በቀጣይ በሚሰማሩበት የሥራ መስክ ሁሉ ሙያዊ ሥነ ምግባርን በመላበስ ሀገራዊ ግዴታቸውን እንዲወጡ አስገንዝበዋል።
ሙስናና ብልሹ አሠራርን በመጸየፍ ለሙያቸው ታማኝ መኾን እንደሚገባም አሳስበዋል።
በዩኒቨርሲቲ ቅይታቸው ያገኙትን የተግባርና የንድፈ ሀሳብ ትምህርት በተግባር በማዳበር ለተሻለ ለውጥ መዘጋጀት ይገባልም ብለዋል።
የሪፍት ቫሊ ዩኒቨርሲቲ ተወካይ ፕሮፌሰር ድሪብሳ ዱፌራ እንዳሉት ዩኒቨርሲቲው ባለፋት ዓመታት በመንግሥት ዩኒቨርሲቲዎች ለመማር ዕድሉን ያላገኙ ዜጎች የትምህርት ዕድል እንዲያገኙ በማድረግ በርካታ ዜጎችን ማፍራት ተችሏል። ተመራቂዎች በቀጣይ በሚሰማሩበት የሥራ መስክ መልካም ሥነ ምግባርን በመላበስ ማኅበረሰባቸውንና ሀገራቸውን እንዲያገለግሉ አሳስበዋል።
ዩኒቨርሲቲው አኹን እየሰጠ የሚገኘውን የትምህርት ዘርፎች በማስፋፋት የመጀመሪያና የሁለተኛ ዲግሪ ተጨማሪ ፕሮግራሞችን ለመስጠት መዘጋጀቱን አንስተዋል።
በየትኛውም ቦታ ሙያዊ ሥነ ምግባርንና የገቡትን ቃል አክብረው ለመሥራት መዘጋጀታቸውንም ተመራቂዎች ገልጸዋል።
ዩኒቨርስቲው ከተጀመረ 2007 ዓ.ም ጀምሮ 1 ሺህ 802 ሰልጣኞችን ማስመረቁን ከዩኒቨርሲቲው ያገኘነው መረጃ ያመለክታል። ቴሌግራም https://t.me/Rift0583209001