21/06/2026
በጎንደር ዩኒቨርሲቲ የሥራ ዕድልና ፈጠራ ልማት ማዕከል (CEED) ለ2018 ዓ.ም ዕጩ ምሩቃን በሥራ ተነሳሽነትና ዝግጁነት ዙሪያ ሥልጠና በመስጠት ላይ ነው፡፡
*************************
የጎንደር ዩኒቨርሲቲ የሥራ ዕድልና ፈጠራ ልማት ማዕከል (CEED) ለ2018 ዓ.ም ዕጩ ምሩቃን ስልጠናውን ከሰኔ 13-14/2018 ዓ.ም በሁሉም የዩኒቨርሲቲው ግቢዎች የሰጠ ሲሆን በዛሬው ዕለት ሰኔ 14/2018 ዓ.ም ፍፃሜውን ያገኛል።
የሥራ ዕድልና ፈጠራ ልማት ማዕከል አስተባባሪ የሆኑት ዶ/ር ገብሬ ሙሉዓለም ስልጠናውን አስመልክተው እንደተናገሩት “ይህ የምሩቃን ሥልጠና በዓላማ-መር ሕይወት (Purpose-Driven Life)፣ ራስን ማወቅና ግላዊ ክህሎትን ማሳደግ ፣ በሥራ ዝግጁነት ክህሎት (Employability Skills) እና በሥራ ፈጣሪነት (Entrepreneurship) ዙሪያ ላይ ያተኮረ መሆኑን አስረድተዋል፡፡
ዶ/ር ገብሬ አክለውም “ይህ ሥልጠና ተማሪዎቻችን ከተለመደው የአካዳሚክ ዕውቀት ባሻገር ወደ ሥራው ዓለም ሲቀላቀሉ ተወዳዳሪና ስኬታማ እንዲሆኑ የሚያስችል ትልቅ ድልድይ ነው" ሲሉ ገልፀዋል። ምሩቃን ወደፊት በቅጥር ላይ ብቻ ሳይወሰኑ በሥራ ፈጣሪነት አስተሳሰብ የታነጹና በሀገር ኢኮኖሚ የራሳቸውን አወንታዊ አሻራ የሚያሳርፉ መሆን እንዳለባቸው አሳስበዋል።
ሥልጠናውን የጎንደር ዩኒቨርሲቲ ከሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ጋር በመተባበር በተሰጠው የዋና አሰልጣኞች ሥልጠና (Master Trainers) የሰለጠኑ 38 አሰልጣኝ መምህራን እየመሩት ይገኛል። የሥልጠናው ይዘትና ዝግጅት ከተማሪዎቹ ፍላጎት ጋር እጅግ በጣም የተናበበ በመሆኑ ተማሪዎች ከተመረቁ በኋላ የሚገጥሟቸውን ተግዳሮቶች አስቀድመው እንዲረዱና በራስ መተማመን እንዲገነቡ ትልቅ ፋይዳ እንዳለው ያነጋገርናቸው አስልጣኞች ገልፀዋል፡፡
በሥልጠናው ላይ የተሳተፉ ዕጩ ምሩቃን በሰጡት አስተያየት ሥልጠናው በተለይ በተግባር ላይ የተመሰረቱ እንቅስቃሴዎች (የበዙበት በመሆኑ ክህሎታችን በተጨባጭ ለመፈተሽ እንደረዳንና ወደ ሥራው ዓለም ለመግባት ትልቅ ስንቅና መነሳሳት ፈጥሮብናል፤ ወደፊትም ይህ አይነቱ ሥልጠና በተቋሙ ተጠናክሮ መቀጠል አለበት” በማለት ገልፀዋል፡፡
የገበያውን ዓለም መሠረት ያደረገው ይህ ሥልጠና ዛሬ ሰኔ 14/2018 ዓ.ም በስኬት ከተጠናቀቀ በኋላ፣ ምሩቃኑ ሰኔ 16/2018 ዓ.ም “ከትምህርት ወደ ሥራ ዓለም” በሚል መሪ ቃል የአሠሪ ድርጅቶችና አምራች ኢንዱስትሪዎች በሚሳተፉበትና በልዩ ሁኔታ በተቋሙ በድምቀት በሚከበረው ዓመታዊ የሥራ ትስስር መድረክ ላይ በንቃት እንዲሳተፉ ዶ/ር ገብሬ ጥሪያቸውን አቅረበዋል።
********
ለልህቀት እንተጋለን.
የዝብ ግንኙነትና ኮሙኒኬሽን ስራ አስፈፃሚ
ሰኔ 14/2018 ዓ.ም.