21/08/2026
«በየዓመቱ የምናከብረው የአሸንድዬ፣ ሻደይና ሶለል በዓላቶች የሴቶች ነፃነት፣ የህዝቦች አብሮነትና የጋራ ማንነት መገለጫችን ናቸው!» የወልድያ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ዱባለ አብራሬ
ነሃሴ 15/2018 ዓ.ም
የወልድያ ዩኒቨርሲቲ ዘወልድ ባህል ማዕከልና የቴክኖሎጂ ሽግግርና ማህበረሰብ ጉድኝት ዳይሬክቶሬት ከወልድያ ከተማ አስተዳደር ባህል ቱሪዝምና ስፖርት መምሪያ ጋር በመተባበር «ባህላችን ድልድያችን፣ አንድነታችን መድረሻችን» በሚል መሪ ቃል የአሸንድዬ ሶለል እና የቡሄ በዓላትን በዛሬው ዕለት በወልድያ ከተማ የባህል አዳራሽ በፓናል ውይይት በደመቀ ሁኔታ አክብሯል።
የእንኳን ደህና መጣችሁ መልዕክት ያስተላለፉት የወልድያ ከተማ አስተዳደር ባህል ቱሪዝምና ስፖርት መምሪያ ኃላፊ ወ/ሮ ነጻነት አምበሳው የባህልና ቱሪዝም ሀብቶች ከሆኑት መካከል በየአመቱ በወርሃ ነሃሴ አጋማሽ የሚከበሩት የልጃገረዶች የነጻነት በዓላት አሸንድዬ፣ ሶለልና ሻደይ ናቸው ብለዋል፡፡
የማህበረሰቡን ባህላዊና ታሪካዊ እሴቶች በሳይንሳዊ ጥናቶች በማበልጸግ ባህላዊ ይዘታቸውን ጠብቀው ሳይበረዙና ሳይከለሱ ለቀጣዩ ትውልድ እንዲተላለፉ ለማድረግና ለማስተዋወቅ፣ ከዩኒቨርሲቲው ጋር ተቀናጅቶ መስራቱ ወሳኝ መሆኑን የገለጹት ኃላፊዋ በዓላቱ ሃይማኖታዊና ባህላዊ ትስስራቸውን ጠብቀው የቱሪዝም መስህብ እንዲሆኑ በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡
በየዓመቱ የምናከብረው የአሸንድዬ፣ ሻደይና ሶለል በዓላት የሴቶች ነፃነት፣ የህዝቦች አብሮነትና የጋራ ማንነት መገለጫችን ናቸው ያሉት የወልድያ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ዱባለ አብራሬ ሲሆኑ እንዲህ ዓይነቶቹ የፓናል ውይይቶች ባህላዊ እሴቶችን ጠብቆ ለቀጣይ ትውልድ ለማስተላለፍና የህዝቦችን አንድነት ለማጠናከር ከፍተኛ አስተዋፅኦ እንዳላቸው ገልጸዋል።
ዩኒቨርሲቲው ላለፉት በርካታ ዓመታት ይህን የባህል ፌስቲቫል በአጋርነት እያገዘ እንደሚገኝ የተናገሩት የወልድያ ዩኒቨርሲቲ ዘወልድ የባህል ማዕከል ዳይሬክተር መምህር ውቤ ታደገ በበኩላቸው እንደነዚህ ዓይነት የማህበረሰብ እሴቶች እንዲጠበቁ፣ እንዲለሙና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት እንዲኖራቸው በሳይንሳዊ ጥናት አስደግፎ በመሰነድ ለቀጣዩ ትውልድ እንዲተላለፉ ለማድረግ ተቋሙ እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡
በወልድያ ከተማ በተካሄደው በዚህ የፓናል ውይይት ላይ በወልድያ ዩኒቨርሲቲ ምሁራን መምህርት እድላም ንጉሴ እና መምህርት ህይወት ፈንታው አማካኝነት የሻዳይ፣ አሸንድዬና ሶላል ፌስቲቫል ታሪካዊ አመጣጥ በሚል ርዕስ የተዘጋጀ ጥናታዊ ጽሁፍ የቀረበ ሲሆን ተሳታፊዎችም የቀረበውን ጥናታዊ ጽሁፍ መነሻ በማድረግ በርካታ ሃሳብ አስተያየቶችን በማንሳት ውይይት ተካሂዷል፡፡
በተመሳሳይ በየዓመቱ በደመቀ ሁኔታ የሚከበሩትን የቆቦ ሶለል እና የላሊበላ አሸንድዬ በዓላትን ምክንያት በማድረግ በየቦታዎቹ የፓናል ውይይቶች የተካሄዱ ሲሆን የወልድያ ዩኒቨርሲቲ ምሁራኖችም በቦታው በመገኘት ለውይይቱ መነሻ የሚሆኑ ጥናታዊ ጽሁፎችን አቅርበዋል።
ዘገባው የወልድያ ዩኒቨርሲቲ ህዝብና አለም ዓቀፍ ግንኙነት ነው፡፡
-------------------------------------------
‹‹አእምሮ ሲከፈት፤ ዓይኖች ማየት ይችላሉ!›› ‹‹ Open Mind, Open Eyes!››
For latest updates, please follow the university official pages: Web site: https://www.wldu.edu.et/
Facebook፡ https://www.facebook.com/WoldiaUniversity
Telegram Channel =https://t.me/Woldia_University
Linkedin = https://t.me/Woldia_University/2985
Tiktok = https://www.tiktok.com/.university?_r=1&_t=ZS-95j0halspeP
P.O.Box = 400Woldia Town, Amhara Region, Ethiopia.